በአማራ ክልል እና በዙሪያው ባሉ የኢትዮጵያ አካባቢዎች ከምርጫ ማግስት በተፈፀመው የዘር ማጥፋት ጥቃት ላይ ያለ ከፍተኛ ስጋት
- AAA-admin

- 2 hours ago
- 4 min read

ከአማራ ማህበር በአሜሪካ (AAA) የተሰጠ መግለጫ
በአማራ ክልል እና በዙሪያው ባሉ የኢትዮጵያ አካባቢዎች ከምርጫ ማግስት በተፈፀመው የዘር ማጥፋት ጥቃት ላይ ያለ ከፍተኛ ስጋት
ሐምሌ 3 ቀን 2018 EC (ጁላይ 10፣ 2026)
ማጠቃለያ
የአማራ ማህበር በአሜሪካ (AAA) በአብይ አህመድ የሚመራው የኦሮሞ ብልጽግና ፓርቲ (OPP) አገዛዝ እና አጋሮቹ የጦር ኃይሎች በአማራ ማህበረሰቦች ላይ የሚፈጸመው የዘር ማጥፋት ጥቃት መቀጠሉን በተመለከተ ስጋቱን ይገልጻል። ከግንቦት 2018 ዓ.ም ሀገራዊ ምርጫ በፊት፣ ማህበራችን በአማራ ማህበረሰቦች እና በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን (EOTC) ተከታዮች ላይ ለረጅም ጊዜ የቆዩ የሰብአዊ መብት ጥሰቶችን ትኩረት የሚጠይቅ ተመሳሳይ መግለጫ እወጥቶ ነበር። ቀደም ሲል የተገለጹት ጥቃቶች ከግንቦት 24 እስከ ሰኔ 23 ቀን 2018 ዓ.ም ውስጥ ከብሔራዊ ምርጫው ጋር ትይዩ ሆነው የተፈጸሙ ሲሆን እና ከምርጫው ጊዜ በኋላም ያለማቋረጥ ቀጥለዋል። በምርጫ የታደሰው ስልጣንም በመላው ኢትዮጵያ የሚታየውን የጸጥታ እና የጥፋት ሁኔታ ከማሻሻል ይልቅ እያባባሰው እንደሚሄድ ይጠበቃል።
በሲቪል ዜጎች ላይ የሚፈጸሙ ጥቃቶች እና ኢሰብዓዊ አያያዝ
ከግንቦት 24 እስከ ሰኔ 23 ቀን 2018 ዓ.ም፤ AAA 62 የሰብአዊ መብት ጥሰት ክስተቶችን መዝግቧል፡፡ ከእነዚህ ክስተቶች 495 ሲቪለ ሰዎች ተጎጂ ሆነዋል፤ ከዚህም ውስጥ 112 ሰዎች ተገድለዋል፣ 134 ሰዎች ቆስለዋል፤ እንዲሁም ሶስት የፆታዊ ጥቃት ክስተቶች ተመዝግበዋል። እነዚህ ክስተቶች በአማራ እና በኦሮሚያ ክልሎች ውስጥ ባሉ 43 ወረዳዎች እና 15 የዞን አስተዳደሮች የተከሰቱ ሲሆን፤ አብዛኛዎቹ ክስተቶች በፌዴራል እና በክልል ደረጃ ባሉ የአገዛዙ አካላት እንደተፈጸሙ የሚያመላክቱ ናቸው። የአገዛዙ አካላት በምስራቅ አማራ እና በኦሮሚያ ክልል ክፍሎች ከኦሮሞ ነፃነት ሠራዊት (OLA) ታጣቂዎች እና በሰሜን ምስራቅ አማራ የትግራይ ሰላም ኃይል (TPF)ን ጨምሮ ኢ-መደበኛ ከሆኑ የታጠቁ ሀይሎች ጋር በመተባበር ይንቀሳቀሳሉ።
ለአብነትም፣ ከግንቦት 23 እስከ 26 ባለው ጊዜ ውስጥ፣ የOLA ታጣቂዎች በምስራቅ አርሲ ዞን በአሴኮ ወረዳ ነዋሪዎች ላይ ተከታታይ ጥቃቶችን ፈጽመዋል፣ ብዙዎች ተገድለዋል፤ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ጠፍተዋል፣ በሺዎች የሚቆጠሩ ተፈናቅለዋል፤ እንዲሁም የመኖሪያ ቤቶች እና በርካታ የአምልኮ ቦታዎች ወድመዋል።
ሰኔ 5 ቀን፣ የTPF ሀይሎች በሰቆጣ ዙሪያ ወረዳ (ዋግ ኽምራ ዞን) ሃሙሲት ከተማ ላይ በፈጸሙት ጥቃት ስድስት ሰዎች ሞተዋል፤ 15 ሰዎች ደግሞ ቆስለዋል። በሚዲያ ዘገባዎች መሠረት፣ የOLA ታጣቂዎች ከክልሉ ወታደራዊ እና የፖለቲካ ባለስልጣናት ጋር በመተባበር በቅርብ ሳምንታት ውስጥ በሰሜን ሸዋ ዞን ደራ ወረዳ በሚገኙ የአማራ ማህበረሰቦች ላይ ሰፊ ጥቃቶችን ፈጽመዋል። በሚዲያ ዘገባዎች መሠረት፣ በእነዚህ ጥቃቶች ከ45 በላይ ሰላማዊ ሰዎች ተገድለዋል፣ 63 የመኖሪያ ቤቶች በእሳት ተቃጥለዋል እንዲሁም በ17 ቀበሌዎች በርካታ የእንስሳት ከብቶች ተዘርፈዋል። ከትግራይ ሕዝብ ነጻ አውጭ ግንባር (TPLF) ጋር ግንኙነት ባላቸው የትግራይ ታጣቂ ሰፋሪዎች በተያዙ የራያ አካባቢዎች፣ ሃይማኖትን ኢላማ ያደረገ ስደት ቀጥሏል። ይህም ከEOTC ጋር ግንኙነት ያላቸውን የሃይማኖት መሪዎች ላይ በማነጣጠር የሚፈጸሙ ተደጋጋሚ ግድያዎች፣ አካላዊ ጥቃቶች፣ አፈናዎች እና ትንኮሳዎችን ያካትታል።
በዚህ ጊዜ ውስጥ፣ AAA በአማራ እና በኦሮሚያ ክልሎች በሚገኙ አምስት ወረዳዎች እና ሶስት የዞን አስተዳደሮች ውስጥ ስምንት የአየር ድብደባዎችን የመዘገበ ሲሆን በዚህም የበርካታ ሲቪል ዜጎች ህይወት የጠፋ ሲሆን ብዙ ትምህርት ቤቶችም ወድመዋል። አብዛኛዎቹ ጥቃቶች የተፈጸሙት በምስራቅ ወለጋ ዞን በሚገኙ ወረዳዎች ሲሆን የአገዛዙ አካላት በአማራ ማህበረሰቦች ላይ ተደጋጋሚ ጥቃቶችን ፈጽመዋል።
የዘፈቀደ እስር፣ ቤተሰቦችን (ህጻናትን ጨምሮ) አፈና እና የግዳጅ ወታደራዊ ምልመላ መጠናከር
ከግንቦት 24 እስከ ሰኔ 23 ቀን 2018 ዓ.ም፣ AAA በአማራ እና በኦሮሚያ ክልሎች በሚገኙ 15 ወረዳዎች እና 10 የዞን አስተዳደሮች ውስጥ የተፈጸሙ 155 አፈናዎችን እና 91 እስራቶችን ያካተቱ 19 ክስተቶችን የመዘገበ ሲሆን እነዚህም በአገዛዙ አካላት እና OLAን ጨምሮ በሌሎች የታጠቁ ቡድኖች እንደተፈጸመ ያመላክታል።
በዚሁ ወቅት፤ የአገዛዙ ኃይሎች ከፋኖ ሀይሎች ጋር የቤተሰብ ግንኙነት አላቸው በሚል መላው የቤተሰብ አባላት ላይ አፈና አጠናክረዋል። ለምሳሌ፣ ሰኔ 3 ፣ የአገዛዙ ኃይሎች በባህርዳር ከተማ ሁለት ትናንሽ ልጆችን ጨምሮ አምስት የቤተሰብ አባላትን አግተዋል። ሰኔ 17 በተፈጸመ ሌላ ክስተት ደግሞ የአገዛዙ ኃይሎች ከ11 በላይ የወረኢሉ ከተማ (ደቡብ ወሎ ዞን) ነዋሪዎችን አፍነው የወሰዱ ሲሆን በተመሳሳይ ሰኔ 22፣ የአገዛዙ ኃይሎች በአንኮበር ወረዳ (ሰሜን ሸዋ ዞን) መሃል ወንዝ ቀበሌ ቢያንስ አራት የቤተሰብ አባላትን አፍነው ወስደዋል። ከተለዩት ተጎጂዎች መካከል፡- ወይዘሮ ይማልዱ ሸዋን ታምሬ (እናት)፣ አቶ ሚንዳ በላይነህ (ልጅ)፣ አቶ ሽመልስ በላይነህ (ሌላ ልጅ) እና አቶ ሙላቱ በቀለ (ሌላ ዘመድ) ይገኙበታል።
በአዲስ አበባ ከተማ እና በአማራ ክልል መካከል በሚገኙ የኦሮሚያ ክልል አካባቢዎች፣ ማንነትን መሰረት ያደረጉ ጥቃቶች በአማራ ማህበረሰቦች ላይ ቀጥለዋል። ለምሳሌ፣ ከሰኔ 6 እና 15 ብቻ፣ የOLA ታጣቂዎች በደራ ወረዳ (ሰሜን ሸዋ ዞን) በተለዩ ክስተቶች 144 ነዋሪዎችን አፍነዋል። ተመሳሳይ ሪፖርቶች ከዞኑ ሌሎች ወረዳዎች፣ ለምሳሌ ከወረ ጃርሶ ወረዳም ተሰምተዋል። በእነዚህ አካባቢዎች፣ የOLA ታጣቂዎች በሕዝብ ማመላለሻ ተሽከርካሪዎች ላይ ተደጋጋሚ ጥቃቶችን በመፈጸም ተሳፋሪዎችንና አሽከርካሪዎችን ኢላማ ማድረጋቸው ተገልጿል። በእነዚህ ጥቃቶችም ሰዎች ለግድያ እና ለቤዛ ገንዘብ ዓላማ አፈና ሲዳረጉ መቆየታቸው ተዘግቧል። እነዚህ ጥቃቶች ብዙውን ጊዜ የጸጥታ ኃይሎች በሚገኙባቸው አካባቢዎች የተፈጸሙ ሲሆን፣ ጥቃቶቹ በመካሄድ ላይ እያሉ ጣልቃ በመግባት ለማስቆም ወይም እንዳይፈጸሙ ውጤታማና ተጨባጭ የመከላከያ እርምጃዎችን ሲወስዱ አይታዩም ተብሏል፡፡
በTPLF ኃይሎች ቁጥጥር ሥር በሚገኙ የራያ አካባቢዎች፣ ነዋሪዎች ለተስፋፋ የዘፈቀደ እስርና አፈና ተጋልጠዋል። እነዚህ ድርጊቶች በትግራይ ሰፋሪዎች አስተዳደር እና በትግራይ ብሔርተኝነት አስተሳሰብ በሚመራው መንበረ ሰላማ በተባለ ሃይማኖታዊ ተገንጣይ ቡድን ድጋፍ እንዳገኙ ተዘግቧል። ከተመዘገቡት ክስተቶች ከፍተኛ ክፍል የEOTC የራያ ሀገረ ስብከት አባል የሆኑ የሃይማኖት አገልጋዮችን ዒላማ ያደረጉ የዘፈቀደ እስሮችን የሚያካትቱ ቢሆንም፣ በአጠቃላይ የአማራ ተወላጆች እየተካሄደ ባለው የግዳጅ ወታደራዊ ምልመላ ጋር በተያያዘ ለአፈና ተዳርገዋል። እነዚህ የዘፈቀደ እስርና አፈና ክስተቶች በአላማጣ ከተማ፣ በራያ አላማጣ፣ በራያ ባላ፣ በኮረም፣ በኦፍላ እና በዙሪያቸው ባሉ ሌሎች አካባቢዎች ተመዝግበዋል።
በወሩ መጀመሪያ በምሥራቅ አርሲ ዞን ከተከሰተው በማንነት ላይ ያነጣጠረ ጥቃት በኋላ፣ የመንግሥት አካላት ለጥቃቱ ተጎጂዎች ፍትሕና ተጠያቂነት እንዲሰፍን ጥሪ ያቀረቡ የሃይማኖት መሪዎችን፣ የሃይማኖት ነፃነት ተሟጋቾችን እና የEOTC ተከታዮችን ዒላማ ያደረገ ሰፊ የእስር ዘመቻ አካሂደዋል። ከግንቦት 30 እስከ ሰኔ 3 ቀን፣ የመንግሥት የጸጥታ ኃይሎች በጎንደር እና በአዲስ አበባ ከተሞች በርካታ ግለሰቦችን አስረዋል። ለምሳሌ፣ ሰኔ 1 ቀን ጋዜጠኛ ሳልሳዊት ባይነሳኝ በግል የማኅበራዊ ሚዲያ ገፆቿ ላይ ባሰፈረቻቸው ጽሑፎች ምክንያት በአዲስ አበባ ከተማ ከመኖሪያ ቤቷ ተይዛ ታስራለች። ከሁለት ሳምንት ገደማ እስር በኋላ መለቀቋ ተዘግቧል። በተጨማሪም ከታሰሩት መካከል ዘመነ ሀብቱ፣ መሪጌታ በትረማርያም አበባው፣ ዲያቆን ዘላለም ታዬ እና ዲያቆን ቤኒ ዘ ጨርቆስ ይገኙበታል።
ከምርጫ በኋላ የተጠናከረ ጭቆና እና የውይይት ዲስኩር
ቀደም ሲል እንደተገለጸው፣ በኢትዮጵያ ነፃ፣ ፍትሃዊ እና ተዓማኒ ምርጫ አልተካሄደም። ምክንያቱም ከፍተኛ ቁጥር ያለው ሕዝብ ለደህንነት እጦትና ለሰብዓዊ ቀውሶች ተጋልጦ ነበር። በአብዛኛው የአማራ ክልልና በዙሪያው ያሉ ሌሎች አካባቢዎች የምርጫ ሂደት ባይካሄድም፣ በተወሰኑ አካባቢዎች ነዋሪዎች በግፍ፣ በማስገደድ፣ በማስፈራራት፣ በተጨባጭ ያልተገባ ገንዘብ መጠየቅ (ከመጠን ያለፈ ቅጣት ማስፈራሪያን ጨምሮ)፣ ከሥራ ማሰናበት ማስፈራሪያ እና ሌሎች ሕገወጥ መንገዶች በመጠቀም የምርጫ ካርድ እንዲቀበሉ ተገደዋል።
ይህም የሆነው የተፎካካሪ ፖለቲካ አካላት አባላት ለሞት የሚዳርግ ጥቃት፣ እስር እና ስደት ሰለባ በሆኑበት በተካሄደ ተቃዋሚ ያልነበረው የምርጫ ሂደት ውስጥ ነበር። ለምሳሌ፣ የፓርላማ አባላትን፣ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላትን፣ የሲቪል ማህበረሰብ መሪዎችን፣ ገለልተኛ ጋዜጠኞችን እና ሌሎችንም ጨምሮ በሺዎች የሚቆጠሩ የፖለቲካ እስረኞች ጉዳይ የሀሳብ ነፃነት፣ የሲቪክ ተሳትፎ እና የሚዲያ ነጻነት አለመኖሩን የሚያረጋግጥ ነው።
ከዚህ ጋር በተያያዘ፣ አገዛዙ በኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን (ENDC) አማካኝነት ብሔራዊ አጀንዳዎችን አስተዋውቋል። ከሁለት ዓመታት በፊት በዓለም ዙሪያ የሚገኙ የሲቪክ ድርጅቶች ENDCን እና በወቅቱ የነበረውን የውሸት ብሔራዊ የውይይት ሂደት ዛሬም ድረስ አግባብነት ባላቸው ምክንያቶች ማውገዛቸው ልብ ሊባል የሚገባው ነው።
ምክረ-ሃሳቦች
የአማራ ማህበር በአሜሪካ በኢትዮጵያ እየታዩ ያሉ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን አዳዲስ አዝማሚያዎች በጋራ ለማውገዝ፣ ተፅዕኖ ፈጣሪ ሀገራት፣ ዓለም አቀፍ ተቋማት እና የሰብዓዊ መብት ድርጅቶች እንዲሳተፉ ጥሪውን ያቀርባል። ይህም በተለይ የOPP ሥርዓትን እና ከእሱ ጋር የተባበሩ ቡድኖችን በቀጥታ ማውገዝን ያካትታል። በተጨማሪም፣ ማህበሩ ዓለም አቀፍ አጋር ሀገራትን እና የገንዘብ ተቋማትን ለተጨማሪ ጥቃቶችና የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ለመፈጸም ሊውል የሚችል የወታደራዊ ቁሳቁስ ግዥን ለመደገፍ የሚውል ማንኛውንም የገንዘብ ድጋፍ እንዲያቆሙ ጥሪ ያቀርባል። እንዲሁም፣ አጋር ሀገራት የሰብዓዊ መብት ክብርን ለማበረታታት፣ በኢትዮጵያ ሰላምና መረጋጋትን ለማስፋፋት እንደ ተጠቃሚ ማዕቀቦች ያሉ የዲፕሎማሲ መሣሪያዎችን እንዲጠቀሙ ጥሪ ቀርቧል።












Comments